2015 ኦክቶበር 7, ረቡዕ

ሎሬት ዘ ገባ ሆሮ !


የአዋሽ ወንዝ አዞ....
ከወንዙ ዳርቻ - ፀሃይ እየሞቀ - ቢያዩት ተዘርግቶ
መሰላቸው ሬሳ - መሰላቸው ዝተት - መሰላቸው ጉቶ
ያረጀ ያለቀ - የደረቀ ቋንጣ - የሞተ ቡቱቶ
(ግጥም - ገቢሳ ሙለታ)
- ተ.ገ. እንደተረጎመው -
ፊንጫሃ ስኳር ፋብሪካ ስንመለስ የመጣንበትን የጌዴዎ
መንገድ በመተው፣ በባኮ - አምቦ መስመር ወደ አዲስ አበባ ተጓዝን።
በግምት ስድሳ ኪሎሜትር ያህል እንደነዳን አንዲት የደከመች መንደር
አጊኝተን እረፍት ሆነ። ፈንታ ተፈራ ሆቴል ደጃፍ ላይ መኪናችንን
አቁመን እስክንወርድ ድረስ ያቺ ደሳሳ ከተማ ማን መሆኗን
አላወቅንም። ሻምቡ ኖራለች። የሆሮጉዱሩ ዋና ከተማ። በባህርዛፎች
ተከባ ተራራ ላይ ጉብ ብላለች።
እነሆ! ስለ ገቢሳ ሙለታ እናወጋለን!
አይነስውሩ አዝማሪ ገቢሳ ዘውድ ያልደፋ የሻምቡ ንጉስ
ነበር። በዚያን እለት ከዚህ ብሩህ ልብ ካለው አዛውንት ጋር ጥቂት
ቆይታ ለማድረግ እድል አጊንቼያለሁ። ርግጥ ነው፤ ገቢሳን በተመለከተ
ከእለታት አንድ ቀን ቁራጭ ወግ እንደምፅፍ ርግጠኛ ነበርኩ። እንዲህ
እዘገያለሁ ብዬ ግን አልገመትኩም።
...በረንዳው ላይ ተቀምጠን ቡና እያጣጣምን ሳለ አባመጋላ
ፈረስ ላይ የተቀመጠ፣ ባላባት የመሰለ ሰው ጎዳናውን ይዞ ሲያልፍ
182
አየን። ጥቁርና ነጭ ነበር ፈረሱ። በእድሜ መግፋት ጥቁሩ እየነጣ ነጩ
በዝቶአል። የፈረሱ ልጓም ጠና ባለ መንገድ መሪ ተይዞ ነበር። ገቢሳ
ጫፉ የሾለ አስኮ ጫማ አድርጎአል። ረጅም ቀይ መልከመልካም ሲሆን፣
ጠጉሩ ጥጥ ይመስላል። ደንዳና ነው። ጋቢውን ጀርባው ላይ ጣል
አድርጎአል። ከጋቢው ስር ቡኒ ጀርሲ ኮት ይታያል። ኮቱ ባለትልልቅ
ቁልፍ እና ባለ አራት ኪሶች ነበር። ይህ ሰው ገቢሳ መሆኑን የሆቴሉ
አስተናጋጅ አጫወተኝ። አስተናጋጁ ጨምሮ ጥቂት አወጋን...
“...በዘመነ ደርግ ታስሮ ነበር። በሰፈራ ስም ጎጆ ሲያፈርሱ፣
‘ጎጆ የሚያፈርስ ቁራ መንግስት’pብሎ በመዝፈኑ ነበር የታሰረው።”
ገቢሳ ስለ እስርቤቱም እንዲህ አቀነቀነ፣
Waaqnii silaa hin dulloomuu- inni utubaan hoomii
Inni sanqaan badessaa
Silaa daanyaan naa hin hiikuu qataroo fagessaa
Alaan zabituu na eegaa qawwee gonbifatee
Kessaan taffituu na eegaa- mangagaa jallifatee
የግጥሙ አሳብ ወደ አማርኛ ሲመለስ እንደሚከተለው ነበር፣
ጎሬው አያረጅም - ጉድጓድ ወህኒ ቤቱ
ብርቱ ነው ምሰሶው - ጥቁር ነው እንጨቱ
ብሳና ነው ሳንቃው - እሳት ነው መሬቱ
ዳኛው ፍርድ አያውቅም...
ቀጠሮ ያረዝማል - አይፈታም ፊቱ
ኮስታራው ዘበኛ...
ጠመንጃ ደቅኖአል - ቆሞ ከደጃፉ
ትሁዋን ከውስጥ አለ - ተባይ ከነ ክንፉ
ደም መጦ ሊጠጣ - በሹላሹል አፉ
ገቢሳ ሶስቱንም ስርአት እየተቃወመ ዘልቆ ነበር። በታሪኩ
ስለተሳብኩ ገቢሳን ቃለመጠይቅ ለማድረግ ፈልጌ ነበር። ለጋዜጠኞች
ቃለመጠይቅ መስጠት እንደማይወድ ነገሩኝ። መሰንቆውን ይዞ
ከሚያቀነቅንበት “ጥሩ ደበላ ጠጅ ቤት”p በመሄድ ሲዘፍን መቅዳት ግን
ይቻላል። አሁንም ወደዚያ ማለፉን ጠቆሙኝ...
መንገደኛ እንደመሆኔ ጊዜ አልነበረኝም። ቢሆንም ወደ ጠጅ
ቤቱ ጎራ ብዬ ገቢሳ ሲያቀነቅን ሰማሁት። ጋዜጠኛ መሆኔን ሳልናገር
ወግ ጀምሬ ገቢሳ ስለራሱ በጨረፍታ አጫወተኝ። እርጅና የድምፁን
183
ሃይል አልጎዳውም። እንደልቡ የመናገር ችሎታ ያለው ሲሆን፣
ባለወፍራም ድምፅ ነበር።
ወላጆቹ ከበቾ ወደ ወለጋ የመጡ የሸዋ ኦሮሞዎች ነበሩ።
ዳዶ ቢርቢርሳ ኮርማ ተወለደ። ቢርቢርሳ ትልቅ የእንጨት ዘር ነው።
ዳዶ የሻምቡ ጎረቤት ናት። ማልዶ ከዳዶ በእግሩ መንገድ የጀመረ
አረፋፍዶ ሻምቡ መግባት ይችላል።
ገቢሳ ዳዶ ላይ እያደገ ሳለ በሰባት አመት እድሜው አይኖቹን
አጣ። የበቆሎ እሸት በልቶ፣ በቆሎ መሃል ስለተኛ አይኖቹን ስለማጣቱ
ነግረውት ነበር። ገቢሳ ግን አሁን ይህን አባባል አያምንም። ፈንጣጣ
ናት ያጠቃችው። ‘ግፍራ’p ይባላል በኦሮምኛ። የ70 አመት አዛውንት
ሲሆን፣ የሚተዳደረው ዘፍኖ በሚያገኘው ገቢ ነበር። በተጨማሪ የሆሮ
ቡልቅ እድር የአመራር አባል፣ እንዲሁም ባለትዳር እና የልጆች አባት
ነው። ገቢሳ አንድ ዜማ አዜመልኝ። ከዚያ በላይ ግን አልቆየሁም።
ተገቢውን ክፍያ ፈፅሜ መንገዴን ቀጠልኩ። አይነስውሩን አዝማሪ
ከመሰናበቴ በፊት፣
“የሻምቡ ንጉስ ይሉሃል።”pብዬው ነበር።
ሞቅ አድርጎ ሳቀ። ሳቁ ሃይል ነበረው።
“ኦሮሞ ንጉስ የለውም። በገዳ ስርአት ነበር የምንተዳደረው።”
ገቢሳ ካዜማቸው መካከል አንዱ እንዲህ ነበር፣
Ganama wuxuu jedhuu -akka saroota isaanii
Galgala gibuu jedhuu- akka ganyoota isaanii
Korokodaan nu yaasuu –akka reóota isaanii
Akka malee nu dhaanuu akka nadhoota isanii
አሳቡን ብቻ በመያዝ እንደሚከተለው ተርጉሜዋለሁ።
ጠዋት ውጡ አሉን - ወጣን በጠዋት
ማታ ግቡ አሉን - ገባን በምሽት
እጃችንን አስረው - እግራችንን አስረው
እንደ ውሾቻቸው፣ እንደ አጋሰሶቹ፣ ልክ እንደ ጠቦት
* * *
ጊዜው 1986 ነበር...
184
ኦህዴድ አዴት (ትግራይ) ላይ የተመሰረተበትን የመጋቢት 17
በአል በመላ ኦሮሚያ ከተሞች እያከበረ ነበር። ሻምቡ ላይም እንዲሁ።
ስለሺ ጎዴ ነበር የክብር እንግዳ ሆኖ በአሉ ላይ የተገኘው።
ገቢሳ ዘፈን እንዲያቀርብ ተጋበዘ።
ታዳሚው ሁሉ ገቢሳ ምን ሊዘፍን እንደሚችል ለማወቅ
በጉጉት ነበር የጠበቀው። ገቢሳ ለረጅም ዘመናት የሆሮ ህዝብ አንደበት
ሆኖ እንደመኖሩ እሱን አለመጋበዝ የማይሆን ነበር። ገቢሳን በመጋበዝ
የሚዘፍነውን ማዳመጥ የሁሉም ፍላጎት ነበር። ስለሺ ጎዴ በውነት ቁም
ነገር ሰራ።
“የሚዘፍነውን አትምረጡለት፣ የፈለገውን ይዝፈን።”p ብሎ
አዘዘ። ይህም በሻምቡ ነዋሪዎች ተሰምቶ ኖሮ ገቢሳ መሰንቆውን ይዞ
ብቅ ሲል አዳራሹ በፀጥታ ተመታ። ስለሺ እንኳ የልቡን ሊናገር
በማይችልበት ዘመን ገቢሳ ብቸኛው ነፃ ሰው ነበር። በዚያን እለትም
በአሉ ላይ ከጠበቁት በላይ የሆሮን ልብ የሚነኩ ሁለት ዜማዎችን ይዞ
ቀረበ።
Ya muraa maqasii
Hintaane yaa Mallasii
Deebite roorroon barasii
(ትርጉም)
በመቀስ እኩል እንደተቆረጠ
እንደሌሎቹ...
የመለስ መምራትም አልሆነም
የቀድሞዋ በደል ቀጠለች
Shura Shurshura Kiyya
Ya Shuraa xinumaaf
Gababbatte - na duraa
Shuraa koo shurshuraa koo
WBO ko hukkuraa koo
ቆላሃቸው አሉ - ልክ እንደ ዳጉሳ
አጨድካቸው አሉ - እንደ ሆሮ ጋርሳ
ነዳሃቸው አሉ - ልክ እንደ ኩርቤሳ
ሹራኮ ሹርሹራ - ሹራ ደበናንሳ
185
(የሹርሹራ ታሪክ ራሱን የቻለ መፅሃፍ ሊወጣው እንደሚችል
ይታመናል። ኢህአዴግ ከኦነግ ጋር ካደረጋቸው ከባድ ውጊያዎች አንዱ
ሹርሹራ ከሚመራው የኦነግ ሰራዊት ጋር ያደረገው ውጊያ ነው። ወያኔ
በቀላሉ የማይገመት መስዋእትነት ከፍሎበታል። ቢሆንም ግን ድል
አድርገዋል። በውጊያው ሹርሹራ ተገደለ። ከመሪያቸው መሞት
በሁዋላም የኦነግ ተዋጊዎች ከሞት የተረፉት ከፊሉ ሲማረክ፣ ጥቂቶች
ግን አምልጠው ተበታትነው አፈግፍገዋል። ሹርሹራ ወለጋ ጫካ ውስጥ
የተገደለው ቶሊና አበራ ከሚመራው የወያኔ ሰራዊት ጋር ሲዋጋ ነበር።
ኦሮሞን በኦሮሞ መምታት የቆየ ስልት ነበር። በሃይለስላሴ ዘመን የዋቆ
ጉቱን እና የጃራ አባገዳን ንቅናቄ የቀጠቀጠው ጃጋማ ኬሎ ነበር። )
ዘፍኖ ሲጨርስ ስለሺ ገቢሳን አስጠራው።
“ገቢሳ! እንዲህ የምትዘፍንለት ኦነግ በህይወት የለም’’ኮ!”
“ስለሺ! ተሳስተሃል። ኦነግ አይሞትም።”
“ባንተ ልብ ውስጥ ነው ያልሞተው።”
“ከልብ በላይ ምን አለ ታዲያ?”
“ገቢሳ! ኦነግን በትክክል ማየት አልቻልክም። ኦነግ ከሻምቡ
ከተማ እንኳ ያነሰ ሆኖአል። ኦነግ ህዝቡ ውስጥና መሬት ላይ የለም።”
“ኦነግ በኦሮሞዎች ልብ ውስጥ አለ።”
“ኦነግ ሞቶአል ብለህ ዝፈንና የወር ደሞዝ ልቁረጥልህ?”
“ዋሽቼ እንደማልዘፍን እያወቅህ ለምን ትጠይቀኛለህ?”
“ስለሹርሹራ የምትዘፍነው ውሸት ነው።”
“ሹርሹራ ጀግና መሆኑን ሁሉም ያውቃል።”
“እኔ የማውቀው ሽፍታ እንደነበር ነው...”
“ትግሬዎቹም ወንበዴ ይባሉ ነበር። አሁን ነግሰዋል።”
“ካንተ በቀር ሹርሹራን ጀግና የሚል ሰው አልሰማሁም።”
“ስለሺ! ጫብሬ ስለሆንክ ላንተ አይነግሩህም።”
186
(ጫብር ሆሮ አውራጃ የሚገኝ የቦታ ስም ሲሆን፣ ነዋሪዎቹ
ጫብሬ ይባላሉ። በምኒልክ ጊዜ ወታደር ሆነው ከጎንደር መጥተው
የሰፈሩ ናቸው ይባላል። ኢህአዴግ ስልጣን እንደያዘ የኦህዴድ አባል
የሚሆን ሰው ማግኘት በመቸገሩ እንደ ጫብር ከመሳሰሉ አካባቢዎች
ኦሮሞ ያልሆኑ ኦሮምኛ ተናጋሪዎችን በብዛት መልምሎ የጎደለውን
የኦህዴድ አመራር ሞልቶበታል። ስለሺ ጎዴ በዚህ መንገድ ለስልጣን
የበቃ ሲሆን፣ ድብልቅ ኢትዮጵያውያን ባሉባቸው እንደ ደብረዘይት እና
ናዝሬት የመሳሰሉ ከተሞች በከንቲባነት እየተሾመ አስተዳድሮአል።
ስለሺ የአቅም እጥረት ቢኖርበትም በወንጀል አይታማም። )
“ኦነግ መቼ ይነግሳል?”pሲል እየቀለደ ጠየቀው።
ገቢሳ ግን በቁም ነገር ምላሽ ሰጠ።
“ቀኑን እኔ አልደርስበትም ይሆናል። አንተ ግን ታየዋለህ።”
“የሻምቡ ሰዎች ያሳስቱሃል። በባዶ አዋቂ አደረጉህ...”
“መበደልህን ለማወቅ ምን እውቀት ያስፈልጋል?”ppp
በዚያን ቀን ከገቢሳ ጋር የሚደረገው ሙግት እንዳልሆነለት
ሲያውቅ ስለሺ ወደ ማስፈራራት ገብቶ ነበር።
“ከንግዲህ ስለ ሹርሹራ መዝፈንህን ብሰማ እገድልሃለሁ።”
ገቢሳ እየሳቀ መለሰለት፣
“እኔን ብትገድል ‘አይነስውር ገደለ’pይሉሃል። ይቅርብህ።”
በርግጥ ስለሺ እንደዛተው ገቢሳን ለህወሃት አሳልፎ
ባለመስጠቱ ያስመሰግነዋል። ገቢሳ ከስለሺ ዛቻ በሁዋላ እስከ ህይወቱ
ፍፃሜ በተመሳሳይ መንገድ ጭቆናን እየተቃወመ በመዝፈን ቀጠለ።
“እነ ጃራ አባገዳ፣ ባሮ ቱምሳ፣ እነ ዋቆ ጉቱ፣ እነ ሌንጮ ለታ፣
እነ ዱጋሳ በከኮ፣ እነ ማሞ መዘምር፣ እነ ታደሰ ብሩ፣ እነ ገለሳ ድልቦ፣
በበቀሉበት አገር ስለሺ ጎዴ ወኪላችን ሆነ።”pእያለ ቁጭቱን ያንጎራጉር
ነበር።
የገቢሳ ካሴት ባይታተምም ብዙ ሰዎች እጅ ገብቶአል።
ዝናውን የሰሙ ኦሮሞዎች አዲስ አበባ ድረስ እያስጠሩ እንዲዘፍን
ያደርጉት ነበር። የገቢሳ ግጥሞች አብዛኞቹ ጭቆናን የሚቃወሙ
187
ናቸው። በደልን በመቃወም የታገሉትን ሰዎች ስም እየጠራ ሰዎች
ከፍርሃት እንዲላቀቁ አነሳስቶአል። ህብረተሰቡን አንቅቶአል። በተለይ
የአብሼ ገርባ ስም ከአንደበቱ አይለይም ነበር። አብሼ ገርባ በምኒልክ
ጊዜ ፀረ ነፍጠኛ ትግል ጀምሮ ሳይሳካለት የተገደለ አርበኛ ነበር። ገቢሳ
በማንኛውም ርእሰ ጉዳይ ላይ ግጥም አፍልቆ የማዜም ልዩ ተሰጥኦ
ነበረው። በህይወት በኖረበት ረጅም ዘመን ውስጥ አንድም ጊዜ ልጆቹ
መንገድ ሲመሩት ያልታየ ሲሆን፤
“አባት እንደመሆኔ እኔ እመራቸዋለሁ እንጂ ልጆቼ መንገድ
አይመሩኝም።”p ይል ነበር ይባላል። በርግጥም ገቢሳ ከልጆቹ ባሻገር
የህብረተሰብ መንገድ መሪ ሆኖ የህይወት ዘመኑን በነፃነት ያጠናቀቀ
አርበኛ ነበር...
ኦቦ ገቢሳ ሙለታ 2009 ላይ እድሜ መግፋት ባስከተለው
ህመም ምክንያት አርፎ እዚያው ከነገሰባት ሻምቡ የቀብር ስነስርአቱ
ተፈፅሞአል። በቀብሩ እለት በሆሮጉዱሩ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ
ህዝብ አስከሬኑን አጅቦት ነበር...




ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ